Saturday, October 5, 2013

ወያኔን ለማስወገድ አስገዳጅ የትግል ስልት ወሳኝ ነው!!!

ከለምለም አንዳርጌ(ኖርዌይ)


ወያኔን ለማስወገድ አስገዳጅ የትግል ስልት ወሳኝ ነው!!!



ላለፉት ሁለት አስርተ አመታት ኢትዮጲያና ሕዝቦ ላይ እንደ መዥገር ተጣብቆ ይህ ነው
የማይባል ግፍና ሰቆቃ ሲፈጽም የኖረው የዘረኛው የወያኔ ስርዓት የእድሜ ዘመኑ ማብቂያ
ጠርዝ ላይ ለመሆኑ ኢትዮጲያን ያህል ሃገርና ህዝብ ከሚመራ ስርዓት የማይጠበቁ የማፍያ
ተግባራቱ ስርዓቱ ያለበት የዝቅጠት ደረጃ ጠቋሚዎች ናችው፡፡ በእድሜ ዘመን መጀመሪያ በስም
እንጂ በተግባር ዴሞክራሲን የማያቀው የአንድ ጎጥ ቡድን ለይስሙላ ባስቀመጠው ህገ-መንግስት
የተካተቱትን የዜጎችን መብት በመሻር ሃገሪቱን የምድር ሲኦል አርገዋታል፡፡ በሃገሪቱ ህገ-
መንግስት መሰረት መብታቸውን አውቀው የተቋቋሙ የሞያ ማህበራትም ሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶች
በራሳቸውም ሆነ በስርዓቱ ተጽእኖ ይህ ነው የማይባል ተግባራት ሳይከውኑ በዘረኛው ስርዓት
እየተኮረኮሙ ይፈርሳሉ አልይም በሞኖፖል በተያዘው የፍትህ ስርዓት ተወንጅለው በግፍ በእስር
ይማቅቃሉ፡፡
ከአመታት በኋላ ፍርሃታቸውን አሸንፈው የወያኔ መናጆ መሆን ይበቃናል ብለው ህገ-
መንግስቱ የሚፈቅድላቸውን መብት ለመጠቀም ከዚህ በፊት ባልተለመደ መልኩ ወያኔን
እምቢኝ እያሉ ያሉት በአገር ውስጥ በሰላማዊ መንገድ የሚታገሉት ጥቂት የፖለቲካ
ድርጅቶች መብታቸውን ተጠቅመው የሚያደርጉት የሰላማዊ ትግል መርህ የዚህን ዘረኛ
ስርዓት ማንነት ፍንትው አድርጎ ያሳየን አጋጣሚ ነው፡፡ ምንም እንኳን የኢትዮጲያ ሕዝብ
ስለወያኔ ማንነትና ምንነት የጠለቅ ግንዛቤ ቢኖረውም በዚህ ደረጃ በወረደና በዘቀጠ ማፊያ
ቡድን እንደምንመራ ማመን በእጅጉ ይክብዳል፡፡
አንድ የፖለቲካ ድርጅት እንደ ድርጅት ምልኡ የሚሆነው የተነሳለትን አላማና እቅድ
እንዲሁም የሕዝብን መሰረታዊ የመብት ጥያቄዎች ተግባራዊ ምላሽ እንዲያገኙ በፅናት
መታገል ሲችል ነው፡፡ እንደ ወያኔ ያለ አምባገነን ስርዓት አፍኖ ለያዘው የሕዝብ የመብት
ጥያቄ ምላሽ የሚሰጠው በተፅኖ እንጂ በችሮታ አይደለም፡፡ ለሚጠየቀው ህገ መንግስታዊ
የሕዝብ ጥያቄ ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጥ አይጠበቅም አምባገነን ነውና፡፡ ስለሆነም መብቱን
የሚያስከብር ለምን?! እንዴት?! በቃኝ፣! እምቢ! የሚል የሕዝብ አደረጃጀት እንዲኖር
የፖለቲካ ድርጅቶች በተገቢው ደረጃ ሕዝብን ማደራጀትና መርሆና፣ እቅዳቸውን ማስረፅ
እንዲሁም ለለውጥ የተዘጋጀ ትግሉን ከዳር ሊያደርስ የሚችል ፍርሃቱን የሰበረ የህብረተሰብ
ሃይል ሊገነቡ ግድ ይላቸዋል፡፡ ይህንን ህዝብ ለትግል በማነፅ የግፍ ቀንበሩን ከጫንቃው ላይ ማውረድ የሕዝብ ወገን ነን
ከሚሉ የፖለቲካ ድርጅቶች የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡ የትኛውም የትግል ስልት አይነቱ
ይለያይ እንጂ ቁርጠኝነትና መስዋትነት ይፈልጋል ስለዚህም አታጋዮቻችን መገንዘብ
ያለባቸው የምንጠይቀው የሕዝብ መብት ወያኔ በችሮታ የሚሰጠን የኛ ያልሆነ ሳይሆን
ሰብአዊ ፍጡር በመሆናችን ልናገኝ የሚገባን እውነታችን እንደሆነ ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ እናም
ለእውነት ዋጋ ለመከፈል ዝግጁነት ያስፈልገናል፡፡ ትግሉ በከረረ ቁጥር ዘረኛው ስርዓት
ማጣፊያ ሲያጥረው ለሚወስደው ማንኛውም እርምጃ መቋቋም በሚያስችል መልኩ ጠንካራ
አደረጃጀት ሊኖረን ግድ ይላል ፡፡
የወያኔ ዘረኛ ቡድን ህገ መንግስቱ የሚፈቅድልንን ለቁጥር የሚታክቱ መብቶቻችንን
ቢነፍገንም፣ ሚያዚያ 30 1997ዓ.ም የነበረውን የቅንጅት የድጋፍ ሰልፍ ተከትሎ ለስምንት
አመታት ቀምቶን የነበረውን ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ህገ መንግስታዊ መብታችንን
ለማስመለስ ከአመታት በሗላ በወጣቶች ለተደራጀው ሰማያዊ ፓርቲ ምስጋና ይግባውና
እጅግ በተጠና ወቅትና ጊዜ የመሰለፍ መብታችንን ከገዢዎቻችን እጅ አውጥቶ በሕዝቡም
ላይ የተጫነውን የፍርሃት ድባብ በመግፈፍ እረገድ ሃላፊነቱን ተወቷል፡፡
ከዚህ አኳያ የረፈደ ቢመስልም በአሁኑ ወቅት በሃገር ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ የሰላማዊ
ትግል እንቅስቃሴዎች ለዘረኛው ቡድን የራስምታት መሆናቸው አያጠያይቅም፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ስኬት ለሌሎቹ እንደ ማንቂያ ደውል በመሆኑ አንድነት ፓርቲም
የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት በሚል መሪ ቃል በክልል ከተሞችና በአዲስ አበባ እጅግ ፈታኝና
ከእልህ አስጨራሽ ትግል በኋላ የተሳካለት ሊባል የሚችል ሰላማዊ ሰልፍ አድርጓል፡፡
99.6 የሕዝብ ድምጽ አለኝ የሚለው የወያኔ ዘረኛ ቡድን በመልካም አስተዳደር ችግርና በኑሮ
ውድነት እንዲሁም በፍትህ መጓደል የተንገሸገሸውን ሕዝብ በመፍራት ሰልፉን ለማደናቀፍ
የቻለውን ያህል ቢጥርም መሰዋትነት ለመክፈል በቆረጡ የድርጅቱ አመራርና ጠንካራ አባላት
ጥረት የታሰበውን ሰላማዊ ሰልፍ ማስተጓጎል ሳይቻለው ቀርቷል፡፡
ይህ የሚያሳየው በነፃነት የመኖር ሰዋዊ መብታችንን በአፋኝ አምባገነን መሪዎች መነጠቃችንን
ነው፡፡ ስለሆነም መብታችንን ለማስመለስ(ለማስጠበቅ) አስገዳጅ የትግል ስልት
እንደሚያስፈልገን አጠያያቂ አይደለም፡፡ በመሆኑም አሁን ያለውን የሕዝብ ለነጻነትና ለትግል
የመነሳሳት መንፈስ በተጠናከረና በተደራጀ መልኩ ለማስቀጠል ቁርጠኛ እርምጃ መውሰድ
ይጠበቅብናል፡፡ በዘረኞች ለሚፈበረኩና ነጻነት የሚነፍጉ ህግጋቶችን እምቢ፣ አሻፈረኝ የሚል
ህዝብ ለመፍጠር የድርጅት አመራሮች ከዚህ በተሻለ በቁርጠኝነት መስራት ይኖርባቸዋል፡፡
ድል ለኢትዮጲያ ሕዝብ!!! http://www.assimba.org/Articles/Woyanen_Lemaswoged_Yetigil_Silt.pdf

ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም የተቃዋሚ ፓርቲዎች ሰልፍ ላይቀጥል ይችላል አሉ

ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚያደርጓቸው የተቃውሞ ሰልፎች ተደጋጋሚና መንግስት አቋም የያዘባቸውን ጉዳዮች የሚያነሱ እንደሆኑ የጠቆሙት ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ፤ መንግስት ለእያንዳንዱ ሰልፍ ጥበቃ ማድረግ ስለማይችል ሰልፎቹ በተለመደው መልኩ ላይቀጥሉ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ትናንት በጽ/ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ የሚያነሷቸው ጥያቄዎች የራሳቸው የፓርቲዎቹ ሳይሆኑ የሌሎች ሃይሎች እንደሆኑ ገልፀዋል፡፡
ፓርቲዎቹ ሰልፍ ማካሄድ ህገመንግስታዊ መብታቸው መሆኑን የጠቀሱት ጠ/ሚኒስትሩ፤ መንግስት በተደጋጋሚ ጥበቃ ሲያደርግ ቢቆይም፣ በሰልፎቹ የሚነሱት ጥያቄዎች ፋይዳ ቢስ ከመሆናቸውና ከፓርቲዎቹ ብዛት አንፃር መንግስት በቀጣይ ለሰልፎች ጥበቃ ለማድረግ የሚቸገርበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ መንግስት በተደጋጋሚ ምላሽ የሰጠባቸውን ጥያቄዎች መላልሰው የሚያቀርቡት በመንግስት ላይ ጫና በመፍጠር አቋሙን ለማስቀየር በማሰብ ሊሆን ይችላል ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ይሄ ግን በፍፁም የማይሳካ ሃሳብ ነው ብለዋል፡፡ “ግንቦት ሰባት” በቅርቡ መንግስትን ለመጣል ወታደራዊ እርምጃ እንደሚወስድ በይፋ መግለፁን በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱም፣ የፓርቲው አመራሮችና ደጋፊዎች ተጨባጭ ያልሆነ ህልም ውስጥ ሆነው የተናገሩት ነገር እንደሆነና ከህልማቸው ሲነቁ እውነታውን እንደሚገነዘቡት ጠ/ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ መከፋፈልና የሃይል መጠባበቅ አለ የሚለውን መረጃ በተመለከተም “ይህ የአንዳንድ አፍራሽ ሃይሎች ከንቱ ምኞትና ተጨባጭ ያልሆነ አሉባልታ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡ addisadmas

የድል ቀን እንዲፋጠን ሁላችንም እጅ ለእጅ ተያይዘን እንነሳ!

ማን ነው የሚለየው? የሚደፍረው?
ይህም ትውልድ ፍም እሳት ነው።
የታለ አንድነቱ…. የፍቅር ተምሳሌቱ?
አረ ጎበዝ…..
እምቢ በል!
እምቢ…. እምቢ…እምቢ…..

የማደንቃቸው ሮቤል አባቢያ ዲሞክራሲ ከደጅ እያንኳኳ ነው በሚለው ጽሁፋቸው ዘመነኛ ቀስቃሽና ነገን አመላካች የሆኑ
የዜማ ርዕሶችን እያደናነቁ የሀገራችንን ትንሳዔ ህልውና አብሳሪ የሆነውን ቀስተደመና መሰል ሰንደቅዓላማ ወጣቶች ከፍ
አድርገው ስለማውለብለባቸው በውብ ብዕራቸው ከኛም አልፎ ሌሎች እንዲረዱት በእንግሊዝኛ አቅርበውት ነበር።
ፕሮፌሰር አለማየሁም ይህንን ከሰጡት በላይ መልሶ ለመስጠት የተዘጋጀን አቦሸማኔ ወጣት ትውልድ አድንቀው ጽፈዋል።
ልሂቃኑ ባሉት ላይ በማከል የሀገራችንን ትንሳዔ በወጣቶቻችን ለነፃነት ቀናዒነትና አልበገር ባይነት እናይ ዘንድ እውነት
መሆኑን የሚያመለክት ከዘረኝነት በላይ፣ ከሀይማኖት ልዩነትም ያለፈ፣ ከፖለቲካ ድርጅቶች አጥርም የዘለለ ሀገራዊ
አንድነቱን ከፍ ያደረገ ማንነትን ሲገልጹ ማየት እጅግ አኩሪ መሆኑን ደግሞ ደጋግሞ መናገር ያስደስታል።
አዛውንቱን አግልሎ ወጣቱን በሉ በሉ የሚል ወይም ወጣቱን አርክሶ ጀግና ድሮ ቀረ የሚል ዘመናትን አገናኝ የሆነውን
ድልድይ አፍራሽና የትውልድን ቅብብሎሽ የሚያረክስ ሀሳብ ስሜታዊ በሆኑ ወገኖች እየተነገረ ሚዛናዊነት ሲጠፋ፣ ተስፋ
ቆራጭነትም ሲስፋፋ ተመልክተን ነበር። ከወጣቶቹ አንዱ ቴዲ አፍሮ “ያለ ትናንት ዛሬ የለም።” እንዳለው መወራረስና
መደጋገፍን ከፍ ማድረጉ አስፈላጊ ነው። ዛሬ ያለው እውነት ትናንት ሆኖ ባለፈው ድርጊት ላይ መሰረቱን ይጥላልና።
ለዚህም ነው በትናንቱ ሁሉን አቀፍ ታሪካዊ ስህተት ተቀፍድደን፣ ዛሬን ሁሉን ነገር ተነጥቀን ላለማለፍ የትናንቱ ስህተት
እንዳይደገም፣ ሸፍጥና መጠላለፍም የነገን ተስፋ እንዳያሳጣን አምቢ በል ለሚሉት ተረካቢ ወጣቶች እውቀትና ብልህነት
በትግሉ ለሰነበቱ አዛውንቶችም ለብሄራዊ እርቅ ብርታትና ጥንካሬን መመኘት ተገቢ የሚሆነው።
የወጣት እድሜ ክልሉ እስከ 30 ከዘለቀ የዛሬዎቹ ወጣቶች በዚህ ምድር በተመላለሱበት ጊዜ ሁሉ ሀገራቸውን እንዲጠሉ፣
በሀገራቸውና በታሪካቸው እንዳይኮሩ የተገደዱና ሀገር ለዜጎችዋ ልትሰጥ የሚገባት ሁሉ ያልተሰጣቸው እንዲያውም
ህልማቸው ስደት፣ ስኬታቸውን በግርድናና ባርነት እንዲለኩ የተገፉቱ ናቸው። የአምባገነኖች አፍራሽ ፕሮፓጋንዳ፣
ጎሰኛነትንና ጥላቻን በሚያስፋፉ ቡድኖች ሁሉ በግድ ጥላቻን በጡጦ የተጋቱት ናቸው በወጣት ቅንፍ ውስጥ ያሉትና ሀገር
ከተረፈችላቸው የነገዎቹ ተረካቢዎች የሚሆኑት። ሀያ ሁለት ዐመት በአዋጅና በተግባር የተደረገው የጥላቻ ዘመቻ ሁሉ ከሽፎ
ክፋትን የዘሩ ቁንጮዎቹ የሰረቁትን እንኳን ሳይበሉ በጠሉት ባንዲራ ተጠቅለው አፈር ሲረግጣቸው ወጣቱ ግን
በመቃብራቸው ላይ ቆሞ ስለሀገሩ ይዘምራል፣ ስለመብቱ ይታገላል፣ ስለነፃነቱም ባደባባይ ይሰለፋል ነፍጥ አንስቶም
ይፋለማል። “ማን ነው የሚለየን?” የሚለው ዘመነኛ ዜማ በቀረርቶ ታጅቦ ሲንቆረቆር ወጣቱ ከትውልድ የወረሰውንና
ለትውልድ የሚያወርሰውን አጣምሮ የተቀኘው ነውና ይመስጣል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ፈጥነውና መጥቀው ዛሬን አልሰጥም ብለው ሀላፊነታቸውን ተቀብለውታል። ርዕዮት አለሙ የዚህ
ምስክር ናት ወጣትነትና ሴትነት ያላገደው ኩራትና ቆራጥነትን በምትከፍለው መስዋዕትነት እያስተማረች በምትክዋ ሺህ
ወጣት ሴቶች በሚያኮራ መንገድ ወደ ትግሉ እንዲቀላቀሉ አርአያ እየሆነች ነው። አንድ ርዕዮትን በምሳሌነት ስንጠራ በሺህ
የሚቆጠሩ በየአደባባዩ ለነጻነት የሚጮሁ፣ በየመድረኩ ለፍትህና ለህግ የበላይነት የሚታገሉ፣ ገንዘብ ጊዜያቸውን ለመስጠት
ወደሁዋላ የማይሉ በርካታ ወጣት ሴቶች በሀገርቤትና በመላው አለምም ተበትነው “ይህም ትውልድ ፍም እሳት ነው….
ኢትዮጵያዊነትን ማን ነው የሚደፍረው ማንስ ነው የሚለያየው እያሉ ነው።” እነርሱ ድምፃቸው ከፍ ብሎ በተሰማ መጠን
ከፋፋዮችና አገር አፍራሾች ሲከፋፈሉና ሲፈርሱ እያየንም ነው። ኢትዮጵያዊነትን መግደል ፈጽሞ አይቻልም የወጣቱ
መነሳሳት የዚህ እውነት ምስክርም ነው። አስተባባሪና መሪ ለመሆን ከመደራጀታችን በፊት ተባባሪ ለመሆን እንዘጋጅ። የትብብር ቁልፉ ከወዲያ ማዶ ያለውንም ወገን ሀሳብ መረዳትና አማካይ መንገድ መፈለጉ ነው። በመድረክ ላይና ከመድረኩ
ጀርባ የሚሰራው የተለያየ ከሆነ ምንም ስም ይሰጠው ትብብሩ የእንቧይ ካብ ይሆናል። በሚናደው የእንቧይ ካብ ውስጥ
መቆጠር ለአጥፊዎች ጉልበት መስጠት ብቻ ነው።
ወጣቶች በየክፍላተ ሀገራቱ እያሰሩና ሀብታቸውን እየዘረፉ መሬታቸውን እየነጠቁ ያሉትን መሳርያ አንስተው እየተፋለሙ
እያገቱና እያደኑ መደፈር በቃ! መረገጥ በቃ! መገዛት በቃ! እያሉ ነው። የትግራይ ወጣቶች በስማቸው ለሚሰራው ግፍ፣
በወገኖቻቸው ዘንድ ጥላቻን፣ መጠራጠርንና መፈራራትን የሚያመጣ ለዘላቂውም በቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጥርስ
እንዲነከስባቸው የሚያደርጉትን ወሮበሎች በግልጽ መቃወም፣ በነፍጥም መፋለም በመጀመራቸው ለጎጠኞቹ የትግራይ
ዘራፊዎች ትግራይ መቀበርያ እንጂ መደበቂያ እንደማትሆን እያሳዩአቸው ነው። በርግጥም ኢትዮጵያውያንን በመከፋፈል
ኢትዮጵያን ማፍረስ እንደማይቻል መረዳት ስለምን አዳገታቸው?
ሰሞኑን በመላው ዐለም የሚታየው ሁኔታ በምስራቅ አፍሪካ ላይ የነጻነት ጮራ እየፈነጠቀ እንደሆነ ነው። የወሮበሎቹ
ተላላኪዎችና አሽከሮች በወጣት ታጋዮች መታደን ጀምረዋል፣ ይህም አስፈሪ እርምጃ ነው። በደቡብ አፍሪካ ለነጮቹ
አድረው ወገኖቻቸውን የሚሰልሉና የሚገድሉትን መክረውና ገዝተውም መመለስ ያልቻሉትን እያደኑ አንገታቸው ላይ ጎማ
አጥልቀው እሳት ይለቁባቸው ነበር። ያ እርምጃ ሆዳሞችን ያሸበረ ዘረኞችን ብቻቸውን ያስቀረ ነበር። የሀገራችን ፖሊሶች፣
የመከላከያ ሰራዊት አባላትም ከዘረኞችና ወርሮ-በላዎች ጉያ በመውጣት ወደ ሕዝቡ በመቀላቀል የሁላችንም የሆነች
ኢትዮጵያን ለመመስረት የሕዝብ ወገንተኛነት ሊያሳዩ ይገባል።
ወጣቶች ትናንትን ትተው ወደፊት እየገሰገሱ ነው። ትናንት የሆነው ሁሉ ለኢትዮጵያ ሲባል የሆነ ነውና አዛውንቱ ቂም
በቀልና መናቆርን፣ ከኔ በላይ ጀግናና አዋቂ የለም የሚለውን እምነትና ያልተወራረደውን ሂሳብ ለመዝጋት ተነጋግሮ ብሄራዊ
እርቅንም ለማምጣት በመጀመርያ ሀገር ሊኖረን ይገባል በሚል መጠላለፉን፣ መካሰሱንና መጠራጠሩን በመተው ይህንን
ሀገር ተረካቢ ወጣት ትናንት በተኬደበት መንገድ እንዳይሄድ፣ እንደ ከሸፉት አብዮቶች በደም ጎርፍ እንዳይታጠብ
የመጨረሻ ሙከራ ማድረጊያው ጊዜም አሁን ነው። በተለያየ የትግል መስክ ተሰማርተው ኢትዮጵያችንን ለመታደግ የቆረጡ
ወጣቶች ተስፋን የሚያለመልሙ የሀገራችንን ሕልውናና ክብር የሚያስመልሱ ናቸው። የ’ፍም እሳቶች’ እምቢ ባይነትና ጽናት
የሚያኮራንም ለዚህ ነው።

የድል ቀን እንዲፋጠን ሁላችንም እጅ ለእጅ ተያይዘን እንነሳ!
ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ በነጻነትና በክብር ለዘላለም ትኑር!

biyadegelgne@hotmail.com